በፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ሁሉም ምድብ ችሎት ለሚገኙ ተጠሪ ዳኞች መጋቢት 10 ቀን 2018 ዓ∙ም በፍርድ ቤቱ ፕሬዝዳንት ፅህፈት ቤት በሚገኘው የመሰብሰቢያ አዳራሽ የፎረም ዉይይት እና የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሃ-ግብር ተከናወነ።
በግንዛቤ ማስጨበጫ መርሃ-ግብሩ የተገኙት የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቱ ፕሬዝዳንት ክቡር አቶ ፉአድ ኪያር ተጠሪ ዳኞች በየምድብ ችሎቶቻቸው ተቀራራቢ የሆነ አሰራር ለመፍጠር መድረኩ ልምድ የምትለዋወጡበት በመሆኑ በቀጣይነት ጠንክሮ መገናኘት እና መስራት እንደሚገባ በማሳሰብ በተለይ አዲስ ተሿሚ ዳኞችም ሆኑ ሌሎች የፍርድ ቤቱ ባለሙያዎች እና ሰራተኞችን በተሻለ ስነ-ምግባር እና በጥብቅ ዲሲፒሊን ወደ ስራ ማስገባት፣ መከታተል እና መደገፍ እንዲሁም በየምድብ ችሎቱ ባልተከናወኑ ተግባራት ላይ ትኩረት አድርጎ ለተሻለ አፈፃፀም መስራት እንደሚገባ ለዚህም የየምድቡ ተጠሪ ዳኞች ተፅእኖ ፈጣሪ መሆን እንደሚገባቸው እና የተግባቦት /የኮሙኒኬሽን/ ክህሎታቸውን ማዳበር እንደሚያስፈልግ ገልፀዋል።
ፕሬዝዳንቱ የተከበሩ አቶ ፉዓድ ኪያር በየምድብ ችሎቶች ለአስተማሪነት የሚሆኑ መገለጫዎችን በማንሳት በተለይ ከስነ-ምግባር ጋር ተያይዞ በአቤቱታ የሚገለፁ ከመዝገቦች መሰወር፣ ከባለ ጉዳዮች መስተንግዶ ጉድለት፣ ከግልፅ ችሎት ወደኋላ የመመለስ ጅምሮች፣ በሰዓት በአግባቡ አለመጠቀም፣ ሚዛናዊ ሆኖ ነገሮችን ሳይጋነንም እንዲሁም ሳያንስም በልኩ በማየት ተከታትሎ መስራት እንደሚገባ በመርሃ-ግብሩ መክፈቻ መልዕክታቸው አሳስበዋል።`